Board of Directorates

ሰበካ ጉባኤ እና ዓላማው

ሰበካ ጉባኤ በተለይ ቅድስት ቤተክርስቲያን ዘመናዊ መዋቅር ያላት ሆና እንድትተዳደር በተደነገገው ህግ ቃለ ዓዋዲ መመስረት ጋር አብሮ የተጀመረ መንፈሳዊ ጉባኤ ነው፡፡ ሰበካ ጉባኤ በቃለ አዋዲ አንቀፅ 5 መሰረት የሚከተሉት አለማዎች አሉት፡፡

  • ቅድስት ቤተክርስቲያንን ለመጠበቅና አገልግሎቷም የተሟላ እንዲሆን ለማድረግ፤
  • የቤተክርስቲያንን አገልጋዮች ሐዋርያዊ ተግባር ለማደራጀትና እንደዚሁም ችሎታቸውንና ኑሮአቸውን ለማሻሻል፤
  • ምዕመናንን ለማብዛት እንደዚሁም በመንፈሳዊ ዕውቀት ጎልምሰው በምግባርና በሃይማኖት ጸንተው በክርስቲያናዊ ህይወት እንዲኖሩ ለማድረግ ፤
  • የቤተ ክርስቲያንን አስተዳደር ለማሻሻልና በማናቸውም ጉዳይ ራሷን ለማስቻል ነው፡፡
  • ከዚህ በተጨማሪ በቃለ ዓወዲው አንቀጽ 6 ላይ ሰበካ ጉባኤው የሚከተሉትን ተግባራት እንደሚያከናውን ተደንግጎ ይገኛል፡፡
  • የእግዚአብሔርን ወንጌል መንግስት ለመስበክና ትምህርቱንም ለማስፋፋት፤
  • መንፈሳዊና ዘመናዊ ትምህርት ቤትን ለማቋቋምና ለማደራጅት፤
  • መንፈሳዊና ማህበራዊ አገልግሎትን ለምዕመናን ሁሉ ለማደረስ፤
  • ሰንበት ትምህርት ቤትን ለማቋቋምና ለማጠናክር ፤
  • የቤተ ክርስቲያን አገልግሎትን ለምዕመናን ሁሉ ለማድረስ፤
  • ለቤተክርስቲያን አገልግሎት የሚያስፈልጉትን ሁሉ ለማሟላት፤
  • የቤተክርስቲያን አስተዳደርና አገልግሎት በቅዱሳት መጻህፍት መሰረት በህግና በሥነ-ሥርዓት ለመምራት፤
  • ቤተ ክርስቲያንን በሀብትና በንብረት በኩል ራሷን ለማስቻል፤
  • የቤተክርስቲያን ሀብትና ንብረት እዳይባክን፣ እየተመዘገበ እንዲጠበቅ፣ እንዲለማና እንዲያድግ ለማድረግ፣
  • ህገ ቤተክርስቲያን በሚፈቅደው መሰረት ከበላይ የሚሰጡትን ህግጋት፣ ደንቦች፣ መመሪዎች፣ ትዕዛዞችና ውሳኔዎች ለመፍጸምና ለማስፈጸም፤
  • በቅርብም ሆነ በሩቅ የሚገኙ ሰበካ መንፈሳውያን ጉባኤያት በማናቸውም ጉዳይ እርስ በእርሳቸው ተባብረውና ተረዳድተው እንዲሰሩ የተቻለውን ሁሉ ለማድረግ፣
  • ልዩ ልዩ የምግባረ ሰናይ ድርጅቶችን ለማቋቋምና አገልግሎታቸውን ለማሟላት፣
  • የህንፃ ሥራ፣ እድሳት፣ ጥገናና የመሳሰሉት ሥራዎች ሁሉ ወቅቱን ጠብቀው የሚፈጸሙበት እቅድና መርሃ ግብር ማዘጋጀት በተግባር መዋላቸውንም ለመቆጣጠር፣
  • የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን እምነት ተከታዮችን ብዛት ፣የሰበካውን ገንዘብና ንብረት ገቢና ወጪ የመሳሰሉትንም እስታቲስቲካዊ መረጃዎችን በወቅቱ እየመዘገቡ በሪፖርት እንዲገለጽ ለማድረግ፤
  • በዚህ ቃለ ዓዋዲ መሰረት ማናቸውንም ቤተ ክርስቲያንን የሚመለከት ጉዳይ ለመፈጸምና ለማስፈጸም፤
  • በዚህ አንቀጽ ከንዑስ አንቀጽ 4 እስከ 14 የተዘረዘሩትን ተግባሮች በቅድሚያ እያጠና ተገቢውን ለማድረግና አስፈላጊም ሆኖ ሲገኝ ጉዳዩ ከሚመለከታቸው ግለሰቦችና ድርጅቶች ጋር እየተነጋገረ ለማስፈጸም፡፡

የደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያንም ቃለ ዓዋዲውን መሰረት በማድረግና የምንኖርበትን ሀገር ህግ (Canada Not-for-profit Corporations Act) በሚያዘው መሰረት የተቋቋመች ስለሆነ በየሁለት ዓመቱ በጠቅላላ ጉባዔው በሚመረጡ ከካህናት፣ ከምዕመናንና ከሰ/ት/ቤት በተውጣጡ አስር አንድ(11) የሰበካ ጉባኤ ሥራ አስፈጻሚ አባላት ትመራለች።

የዳይሬክተሮች ቦርድ

የሰበካ መንፈሳዊ አስተዳደር ጉባኤውም ተጠሪነቱ ለጠቅላላ ጉባኤው ሲሆን የሚከተሉት የስራ ክፍሎች አሉት፡


፩ኛ) የሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤት (የቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ ፣ ም/ሊቀ መንበርና ጸሐፊውን ያቀፈ)
፪ኛ) የስብከተ ወንጌል ማስተባበሪያ ክፍል
፫ኛ) የልማትና ማህበራዊ ማስተባበሪያ ክፍል
፬ኛ) የገንዘብ ቤት
፭ኛ) የሂሳብ ስራዎች ማስተባበሪያ ክፍል
6ኛ) የንብረትና ማስተባበሪያ ክፍል
7ኛ) የህንጻ ጥበቃ ማስተባበሪያ ክፍል
8ኛ) የሰንበት ት/ቤት ማስተባበሪያ ክፍል እና
9ኛ) የቁጥጥር ክፍል ናቸው።

በነዚህ ክፍሎች ስርም እንደየስራው አስፈላጊነት በርካታ ኮሚቴዎች ተቋቁመው እንደእግዚአብሔር ፈቃድ ስራቸውን እያከናወኑ ይገኛሉ። ይህ አወቃቀርም ምዕመናን በችሎታቸው በቤተ ክርስቲያን አስተዳደር መሳተፍ እንዲችሉ የሚያደርግ ሲሆን ዳር ቁመን የምንመለከተው ወይም እገሌ ይሠራዋል፤ በሚል ልንሸሸው የማይገባ፣ ተሳታፊ በመሆን በረከት የምናገኝበት እና የቤተ ክርስቲያን ችግር የሚቀረፍበት መዋቅር ነው፡፡ በመሆኑም የሚጠበቅብንን የድርሻችንን ካልተወጣንና ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅመውን በወቅቱ ካላደረግን ደንቡና መዋቅሩ ብቻውን ትርጉም ሊኖረው ስለማይችል በተሰጠን ጸጋ ልናገለግል ይገባል፡፡ እግዚአብሔርም ከእኛ ብዙ ይጠብቃል፡፡ የተቀበልነው መክሊት ነውና በተሰጠን መጠን ይፈለግብናል /ማቴ. 25-14-30፡፡

የደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን የሰበካ ጉባኤ የተርም 2018 – 2020 መጨረሻ ድረስ የሚያገለግሉ፤

  1. መላከ ጽዮን ቀሲስ ጌቱ ረጋሳ (የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ፤ ሊቀ መንበር)
  2. ዶ/ር ዘሪሁን ደምሴ (ም/ሊቀ መንበር)
  3. አቶ ዘርአይ ደሰይ (ዋና ጸሐፊ)
  4. ዲ/ን ኢዮብ ሃይሌ (የስብከተ ወንግጌል ማስተባበሪያ ክፍል)
  5. ወ/ሮ አበባ ሃይሉ (የልማትና ማህበራዊ ማስተባበሪያ ክፍል)
  6. ወ/ሮ በርኽ ተክለሃይማኖት(የገንዘብ ቤት)
  7. አቶ ቶማስ ሃብተማርያም (የሂሳብ ስራዎች ማስተባበሪያ ክፍል)
  8. አቶ ዮሴፍ ሃይሉ (የንብረትና ማስተባበሪያ ክፍል)
  9. አቶ ዘገየ ሃይሉ (የህንጻ ጥበቃ ማስተባበሪያ ክፍል)
  10. አቶ ሰለሞን ታምራት (የሰንበት ት/ቤት ማስተባበሪያ ክፍል)
  11. አቶ ዮሃንስ ጌታነህ (የቁጥጥር ክፍል) ናቸው።

ወስብሃት ለእግዚአብሔር!